YOUNGERVERSION

just a free corner

ሰኞን አታድርገኝ

ሰኞን በአይምሮዬ ስስለው እድለቢስ ልጅ ይመስለኛል-የመጀመሪያና እድለቢስ ልጅ፡፡ ይሰራሉ የሚባሉትን ስህተቶች ሁሉ ሰርቶ ዋጋውን እየተቀበለ ለሌሎች ምሳሌ የሚሆን ምስኪን መቀጣጫ ልጅ ፡፡ እንደዚህ አይነት ሰዎችን ማግኘት ከባድ አይደለም ፡፡ በእለት ተእለት ህይወታችን ውስጥ ከበቂ በላይ በሚባል ቁጥር በዙሪያችን ይገኛሉ ፡፡ በቀላሉ እንድንለያቸው የሚያስችለው ዋና ባህርያቸው ደግሞ በሞክሮ ማየት (trial and error) የሚያምኑ መሆናቸው ነው፡፡ ማንኛውንም ነገር ከመሞከር ወደሁዋላ አይሉም በአጭሩ ተንቀሳቃሽና የሚተነፍሱ ቤተሙከራዎች ናቸው ፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥ የትኛውም ጉዳት ሊያጋጥማቸው ይችላል መውደቅ መሰበር ማዘን መቆዘም ማልቀስ የግላቸው ሲሆን አንዳንዴ ጉዳቱ ሞትምንም ይጨምራል (ስጋዊ ሞት ማለቴ ነው የመንፈሱንማ እግዜር ይቁጠረው) ዕያንዳንዱ ቀን የራሱ ደስታም ሆነ ውርደት አስከትሎባቸው እንጂ ባዶ እጁን አይመጣም አነሱም አያርሜ በመሆናቸው ሁሉን እንዳመጣጡ ያስተናግዱታል፡፡ እኔም ብሆን ጉዋደኛ-ብዙ ነኝና በርካታ ሰኞዎች ያጋጥሙኛል፡፡ከነሱም ውስጥ አንዱዋ ወዳጄ ትገኝበታለች፡፡ይህች ልጅ አንዲት ሴት ትሰራዋለች የሚባሉትን ስህተቶች ሁሉ በአይኔ በብረቱ እያየሁዋት በየእለቱ ትፈጽማለች፡፡ገና በጠዋት እግርዋ ከቤት ሲወጣ እናትየው በስጋት እስከውጭው በር በአይናቸው ይሸኟታል አባትየውም ቢሆኑ አፋቸው አያርፍም ፡፡ ምንም እንኩዋን ለውጥ እንደማያመጡ ቢያውቁትም ለበሁዋላ “ብዬ ነበር“ እንዲያመቻቸው የጎሪጥ እያዩዋት “ዛሬ ደግሞ ምኑን ጉድ ልታመጪ ይሆን አረ ተይ አንቺ ልጅ ረጋ በይ!“ ብለው ስራቸውን ይቀጥላሉ ለነገሩ ንግግሮቹ በልጅትዋ የየቀን ህይወት ውስጥ የሚደጋገሙ ስለሆኑ ልብ ብላውቸም አታውቅ እውነቱን እንነጋገር ከተባለም እሱዋ ምንም ጥፋት የለባትም :: ቢኖርባትም አንድ ብቻ ነው ፡፡ ሰዎችን ከእግዚአብሄር በላይ ትወዳለች (ታመልካለች ማለቱ ይቀላል) ታዲያ እነዚሁ ተወዳጅ ሰዎች ለፍቅሩዋ ምላሽ ጥላቻን ለታማኝነትዋ ክህደትን በዚሁ ለተጎዳ ስሜትዋ ደግሞ መርዝ ቃላትን ያበረክቱላታል፤፤እዛው አጠገብዋ የነበርኩት እኔ ደግሞ ስታለቅስ እንባዋ ተረጭቶብኝ በንዴት ግርግዳ ስትቡዋጥጥ ጆሮዬን ሰቅጥጦኝ በብስጭት የቤት እቃዎችዋን ስትሰባብር በሱዋ መንገድ ዝር ላለማለት ምዬ ነበር (ምንም እንኩዋን መሃላዬን ባልጠብቅም)
ከሰኞ በአንድ እርከን እድል ከፍ የሚለው ማክሰኞ ከሰኞ አይቶ የተማራቸው ብዙ ነገሮች እንዳሉ ያስባል፡፡ማክሰኞ ሲናገሩት አይወድም፡፡ ማክሰኞ አትንኩኝ ከሰኞ እሻላለሁ ፃዲቅ ነኝ ባይ ነው፡፡ ይሄ ምስኪን ትንሽ አውቆ ብዙ የሚያውቅ ስለሚመስለው አራሱን የተሸለ አርጎ የሚቆጥር ፣የሰኞን ስህተቶች ቆሞ ለማየት ትእግስት የሌለው፣ በሰኞ የቀሩትን ስህተቶች ከሞላ ጎደል እየሰራ ከነውጤታቸው የሚቀፈቅፍ ከወንድሙ ያልተለየ እድለ ሰንካላ ነው፡፡ማክሰኞዎች በዛ ሲሉ ደግሞ በጣም አስቂኝ ናቸው ዋናው መገለጫቸው ጥራዝ ነጠቅ አስተሳሰባቸውና ከልክ ያለፈው በስህተታቸው የመተማመን ባህሪያቸው ነው (እርስ በርስ አለመስማማታቸውም ሌላው ታርጋቸው መሆኑ አይዘንጋ ሁሉም አዋቂ ስለሆነ ጥል የማይቀር ጉዳይ ነው) እነዚህ ሰዎች ሰኞዎችን ሰብስበው ማስተማር ወይም የሕይወት ልምዳቸውን ማካፈል ሊቃጣቸውም ይችላል ፡፡ ሁሌ የሚያስቡት ከሰኞ መሻላቸውን ብቻ ነዋ (ጌታ ሆይ እንደዚያ ቀራጭ ስላላረከኝ አመሰግናለሁ አንዳለው ነው ሰውየው)

በዚሁ ሁኔታ ቀኖቹ አልፈው አርብ ጋር ሲደርሱ ነገሮች ይለወጣሉ፡፡ ከማየት ብቻ የተማሩ፤ ሳይጣዱ የበሰሉ፤ የነሰኞን ግብር ከነደሞዛቸው ያሰሉ ተጠራጣሪና ንቁ ልጆች ናቸው አርቦች ፡፡ እነዚህን ልጆች እድል ከሑዋላ አሰልፋቸው መሰንበት ጠንካራ ምሽግ አስጠግታቸው ጦርነቱን እጅእጅ እስኪላቸው አሳይታቸዋለችና መቼም ቢሆን ድብልቅልቁ ውስጥ ለመግባት አይከጅሉም የሩቅ ታዛቢዎች ናቸው፡፡ በእርሻ ምጣኔ ሀብት ጥናት ላይ ከልክ በላይ ክፉን የሚፈሩ ገበሬዎች (risk-averse peasants) እንዳሉ ይነገራል ገበሬዎቹ ከሌሎች ጎረቤቶቻቸው ተለይተው የሚታወቁት ለትርፍ ከሚንቀሳቀሱና ችግርን ከማይፈሩ ገበሬዎች (risk-prone peasants) በተለየ መልኩ ከችግር የተጠበቁና የምግብ ዕጥረት የማይነካቸው በመሆናቸው ነው፡፡ እርግጥ ነው ትርፍም ኖሩዋቸው አያውቅም ግን መቼም አይጎድላቸውም፡፡ በአብዛኛው ከአካባቢያቸው ኗሪዎች አንጻር ደግሞ ኑሮዋቸውም በመካከለኛ የገቢ ደረጃ የሚገመት ነው፡፡ ጎረቤቶቻቸው ተርፎዋቸው ሲንበሸበሹም ሆነ የምግብ እጥረት ሲያጋጥማቸው እነዚህኞቹን ጉድለቱንም ሆነ ትርፉ አያሳሳቸውም ፡፡ ምክንያታቸው በሌሎች ላይ ሲደርስ የሚያዩት ነገር እንዳይደርስባቸው ያላቸው ፍራቻ ብቻ ነው ፡፡በየእለቱ የሚታዩዋቸው የሚከብቡዋቸው ፍራቻዎች ብቻ ናቸው (የአየር ጸባይ ለውጥ ፍራቻዎች የጸረ እህል ተባዮችና የሌሎች በሽታዎች ፍራቻዎች፡የተፈጥሮዊ አደጋ ፍራቻዎች የመንግስት ጣልቃገብነት ፍራቻዎች የገበያ አለመረጋጋት ፍራቻዎች የመሬት አገዛዝ ስርአትና አልፎ አልፎም የጦርነት ፍራቻዎች) ተደማምረው እነዚህን ገበሬዎች ከመጠን ያለፈ ጥንቃቄ ማድረግን አስተምረዋቸዋል ስለዚህ ሰዎቹን ከትርፍ ይልቅ የመኖር ሀሳብ ያጉዋጉዋቸዋል ለተሻለ ገቢ ሲሉ የቤተሰባቸውን ህይወት አደጋ ላይ መጣል ፈጽሞ የማያስቡት ነገር ነው ከጎረቤቶቻቸው ደህና አርገው ተምረዋልና፡፡

““ሰኞን አታድርገኝ” ይላሉ” አሉ ብልጣብልጦቹ አባቶቻችን፡፡ ለልብ የሚዘልቅ ተማፅኖ ነው ፡፡ ተራቾቹ የሰው ልጅ እጣ ፈንታ ጉዳይ፡ ስሜታቸውን ይሞግት ሃሳባቸውን ይጠይቅ እንደነበር አልጠራጠርም፡፡እንኩዋን እነሱን ቀርቶ ሳይንስ ብዙ ጥያቄዎቻችን መልሱዋል የህይወት ቁዋጠሮዎቻችንንም ፈትቱዋል ተብሎ በሚታሰብበት በ20ኛው ክፍለዘመን የተወለድኩትን እኔን እንኩዋን “በሰው ልጅ ህይወት ውስጥ እድል ቦታ አለው ወይ?” የሚለው ጥያቄ ሲከራከረኝ ኖሩዋል፡፡የአንዳንድ እድለቢሶች የተጣመመ የህይወት መስመርና የአንዳንድ እግረ እርጥቦች ማይታመን እድል ጥያቄውን ደግሜ ደጋግሜ እንድጠይቅ አድርጎኛል፡፡የመጨረሻው መልስ ግን አጭርና ግልጽ ሆኖ ነው ያገኘሁት ፡፡ ዛሬ እኔ በእድል አምናለሁ፡ እንደ አልበርት አንስታይን ከሆነ ደግሞ ሶስቱ የስኬት መርሆች እድል፣ ስራና አፍን መዝጋት ናቸው፡፡
እኛ የአዲስ ኪዳን ሰዎች የሰዎችን ህይወት አይተን ብቻ ያለምንም ጉዳት ዕንድንማር እድሉ በቅዱስ ቃሉ ተሰጥቶናል፡፡በመፅኃፉ በጉልህ የተሳሉት የእግዚአብሄር ሰዎች በክብራቸው ብቻ ሳይሆን በውድቀታቸውም በጽድቃቸው ብቻ ሳይሆን በስህተታቸውም በደስታቸው ብቻ ሳይሆን በሃዘናቸውም የኛን ሽንፈት አትድገሙት እያሉ ዛሬም ይጮሃሉ፡፡ እንካችሁ እድል ይሉናል፡፡ እና ከኛ በላይ እድለኛ አለ? ከኛ በላይስ የአርብ ገድ የተሰጠው ከቶ ማን ነው?
በእውነተኛ አይኖች ስንታይ ግን አብዛኞቻችን ማክሰኞን ነው የምንመስለው፡፡ ወይ እንደሰኞ ተጎድተን አናስተምር ወይ እንደአርብ አይተን አንማር፤ወይ ቆመን አናይ ወይ አንሮጥ፤ ወይ አናዳምጥ ወይ አንናገር፤ ከሁለት ያጣን የሁሉ ባይተዋሮች ፤ ዝም ብሎ ላስተዋለን ደግሞ ቀለም የለሽ አመድማ ፍጥረታት ነን ፡፡ ካልወደቅን መማር ካልተሰበርን መመለስ አቅቶናል ፡፡ሁላችንም አስተማሪ ሁላችንም አዋቂ በመሆናችን ተሳሳትኩ ከመዝገበ ቃላታችን ተሰርዞ ጠፍቱዋል፡፡ በዚሁ ከቀጠልን ገጣሚው እንዳለው ለሲኦል የማንመጥን ለገነት የማንበቃ ተንጠልጣይ ሰዎች እንዳንሆን እፈራለሁ፡፡ ከኛ የማይሻሉትን እያሰብን የአያቶቻችንን ተረት ተርተን ሳንጨርስ ልጆቻችን “ማክሰኞን አታድርገኝ” ብለው በኛው ላይ እንዳይተርቱብንም እሰጋለሁ፡፡

June 30, 2008 Posted by meseret | articles, mesi | | 4 Comments